መሠረታዊ ኦርቶዶክስ አስተምህሮ

 

"ክርስቶስ ተነስቷል!"

 ምንጭ: http://mysteryandmeaning.blogspot.com

 

 

ጸሐፊ ፓቭሎስ ኒርቫናስ
" ስቲያ" ጋዜጣ ላይ የታተመ: አቴንስ 24/11/1937.
ምንጭhttp://genesis.ee.auth.gr/dimakis/neaest/Neaestia.html

** ጽሑፉ በአማርኛ በትንሹ ተስተካክሏል

 

ከብዙ ዓመታት በፊት  በትንሽዋ ተራራማ መንደርፔሎፖኒሶስፋሲካንናትንሣኤ በዓላት ለማክበር በተገኘሁበት ጊዜ በተዘረጋ ክንዳቸው የተለኮሰ የፋሲካ ሻማን የትንሣኤውንሌሊት ሰማይ ወደ አስዋቡት ከዋክብት ከፍ አድርገው የያዙ አንድ በዕድሜ የገፉ የመንደሩን ነዋሪ ተመለከትሁ፡፡ አረጋዊውም እኔን የሚያናግሩ በሚመስል ሁኔታ በለሆሳስ "ልጄ በዚህች ሌሊት ሰማያት ተውበዋል" ሲሉ ሰማሁዋቸው፡፡ 

እኒያ ቅን የመንደሩ ነዋሪ እጅግ ጥልቅ ትርጉም ያለውን የክርስትናን ተአምር በነዚያ አጭር  ቃላት ውስጥ ቅልብጭ አድርገው አስቀምጠውታል፡፡ ታላቁ የክርስትና ተአምር ትንሣኤ ባይኖር ኖሮ ሰማያት ለብዙዎች የአስፈሪውና ለኃጢአት ሁሉ ቅጣትን የሚያመጣው አምላክ ማደርያ ብቻ መስለው በቀሩ ነበር፡፡ 

ወደ ሰማይ ከፍ ያለችው የአረጋዊው ሻማ ለሚብልጨለጩት ከዋክብት ሰላምታ የምትሰጥ የምትመስልበት ያ ጸጥ ያለው የጸደይ ሌሊት በእውነትም ሰማያት የተዋቡበት ይመስላል፡፡ ሰማያት ከዚህ በኋላ ለሕዝቦቹ የማይታወቅና ሩቅ በሆነው አስፈሪ መንበሩ ላይ የተቀመጠ አምላክ ማደርያ መስለው መታየታቸው ቀርቷል፡፡ አሁን ፍቅሩን የገለጠ፣ የሰው ልጅ የተሰቃየውን ስቃይ ሁሉ የተሰቃየ፣ የዓለምን ኢፍትሐዊነት የቀመሰ፣ ሁሉንም ዓይነት መከራ የተመለከተና ስለ ሁሉም ዓይነት ክፋት ዋጋን የከፈለ አምላክ ማደርያ ናቸው፡፡ እርሱ ጥቃት ደርሶበታል፣ ተሹፎበታል፣ ተተፍቶበታል፣ እንደ ክፉ ወንጀለኛ ታስሮ በጎዳና መሬት ለመሬት ተጎትቷል፣ ተሰቅሏል፡፡ ተርቧል፣ ተጠምቷል፣ አስፈሪውን ሞትንም ሞቷል፡፡ ያልታመመው ሕመም ያልደረሰበት ስቃይ ያላሳለፈው መከራ የለም፡፡ ሰው በዚህ ምድር ሊጠጣ የሚችለውን መራራ መጠጥ ጠጥቷል፡፡ ከዛም ልክ እንደዚህ ባለች ሌሊት ወደ ሰማያት አርጎ ይገዛና በዓለም ሁሉ ይፈርድ ዘንድ በአባቱ ቀኝ ተቀምጧል፡፡ ታዲያ አሁን ቀላያትን ፍጹም የሆነ መልካምነት ከቧቸዋልና ሰማያት እንደምን አይዋቡ!

አረጋዊው ‹ከእንግዲህ ወዲህ ኃጥእ ለምን በፍርሃት ይርበተበታል?› ብለው ሳያስቡ አልቀሩም፡፡ ‹ያ ዘማዊቷን ሴት፣ በግራ የተሰቀለውን ፈያታዊ ዘየማንን እና የሰቀሉት ሳይቀር የማረው አሁንም በሰማያት ሆኖ የኃጥኡን የንስሓ እንባ ተመልክቶ ይምረዋል፡፡ የታመመ ሰው ለምን ተስፋ ይቆርጣል? ያ ዐይነ ሥውራንን እና አካለ ስንኩላንን የፈወሰው ከላይ ሆኖ ያያል ይፈውሰዋልም፡፡ ደሀውና የተበደለው ለምን ቅሬታ ይሰማዋል? በምድር ሳለ የተራበውና የተጠማው ይመለከተዋል ያዝንለታልም፡፡ እናትስ ለምን ስለልጇ ትጨነቃለች? የእናትነትን መከራን የምታውቅ፣ ዓለማትን ሁሉ ከሚገዛው ልጇ ለተጨነቁት ምሕረትን የምትለምን አዛኝ እናት በሰማያት አለች፡፡ ወደ ሞት የተቃረበውስ ከሞት የተነሣ ለምን ይፈራል? እንደማንኛውም ነፍስ ለእርሱም ትንሣኤ አለለት…›

በእርግጥም ሰማያት በዚያ የጸደይ ሌሊት የተዋቡ ነበሩ፤ የአረጋዊው ሻማም ወደነዛ ከዋክብት የተነሣው ለሰላምታና ለምስጋና ነበረ፡፡

‹ክርስቶስ ተነሥቷል አባቴ›

‹እርሱ አማላክም ጌታም ነው ልጄ›

ዝግጅት በ: ጋ. እ.